የወላይታ ዞን ዜና
-
የህግ ታራሚዎች ጤንነታቸው የተጠበቀና አምራች ዜጎች እንዲሆኑ ስፖርታዊ እንቅስቃሴ ወሳኝ መሆኑ ተገለጸ ስፖርት ለሁሉም በሁሉም ሥፍራ በሚል መሪ ቃል የወላይታ ሶዶ ማረሚያ ተቋም የህግ ታራሚዎች በጋራ የአካል ብቃት እንቅስቃሴ አካሄዱ። የ2016 ዓ.ም የወላይታ ሶዶ ማረሚያ ተቋም የህግ ታራሚዎች ልዩ ልዩ ስፖርታዊ ውድድር ተካሂዷል። የወላይታ ዞን ወጣቶችና ስፖርት መምሪያ የወጣቶች ዘርፍ ኃላፊ አቶ ወንድሙ ደረጀ የስፖርት ውድድሩን በአካል ብቃት እንቅስቃሴ ያስጀመሩ ሲሆን ታራሚዎች ጤንነታቸው የተጠበቀና አምራች ዜጎች እንዲሆኑ ስፖርታዊ እንቅስቃሴ ወሳኝ ነው ሲሉ ገልጸዋል። አቶ ወንድሙ አክለው ስፖርት አንድነትና እርስ በርስ ያለን ግንኙነት እንዲጠናከር የሚያደርግ እንደሆነ በማስረዳት የሥራ መፍጠሪያም ዘርፍ በመሆኑ የህግ ታራሚዎች ከዚህ ሲወጡ በተሰጥኦዋቸው በመሳተፍ የነገ ተወዳዳሪ ዜጎች ለመሆን በተዘጋጁ ስፖርታዊ ውድድሮች እንዲሳተፉ ጥሪ አቅርበዋል አቶ ደለለኝ ደቻሳ በመምሪያው የስፖርት ዘርፍ ቡድን መሪ ሲሆኑ በስፖርት ፖሊሲው ማንኛውም ዜጋ ስፖርታዊ እንቅስቃሴ መሥራት እንዳለበት በተቀመጠው መሠረት ለህግ ታራሚዎች ስፖርታዊ ውድድሮች መዘጋጀታቸውንና ስፖርት በመሥራት ጤናቸውን እንዲጠብቁ አንስተዋል። በቀጣይ ቀናትም የመረብና የጠረጴዛ ቴኒስ ውድድሮች እንዲሁም ከባህል ስፖርት የገበጣና ገመድ ጉተታ ውድድሮች የተዘጋጁ መሆናቸውን የገለፁት አቶ ደለለኝ የህግ ታራሚዎች በዞኑ በሚደረጉ ልዩ ልዩ የስፖርት ሻምፒዮናዎች በመሳተፍ ከተቋሙ በሚወጡበትም ጊዜ አምራችና ጤናማ ዜጎች እንዲሆኑ እንደሚያስችላቸው አብራርተዋል። በተቋሙ የስፖርት ዘርፍ ባለሙያ የሆኑት ኢንስፔክተር መስፍን ጀጎሌ በተቋሙ ያሉ ዜጎች ነገ ኅብረተሰቡን ሲቀላቀሉ ጤንነታቸው የተጠበቀ እንዲሆን ስፖርት አስፈላጊ መሆኑን በመግለጽ ላመቻቸው የዞኑ ስፖርት ምክር ቤት ምስጋና አቅርበዋል። ስፖርት ሰላም፣ ፍቅር አንድነት ነውያሉት ኢንስፔክተር መስፍን ነገ ለሀገር ልማት አስተዋጽኦ የሚያበረክቱ ወጣቶች እንዲወጡም ያስችላል ብለዋል። ስፖርት በጤና ላይ የሚመጡ በሽታዎችን እንደሚከላከልላቸው ያነሱት ታራሚዎች ታርመን ስንወጣም በልማቱ እንድንሳተፍ ያስችለናል ሲሉ ገልጸዋል። የስፖርት እንቅስቃሴ ከሱሰኝነት፣ ከስሜታዊነትና ከወንጀል ነፃ እንዲሆኑ እንደሚያደርግም ስፖርት ሲሠሩ የዞኑ መንግስት ኮሚዩኒኬሽን ያነጋገራው ታራሚዎች ገልጸዋል።
October 15, 2023